«ያሬዳዊው» ኤልያስ መልካ

ግጥሞች፣ታሪኮች፣ፎቶዎች፣ሙዚቃዎች
Poems,Short stories, graphics,pictures,musics,Technology
Post Reply
selam sew
Leader
Leader
Posts: 690
Joined: 08 Feb 2011 11:14
Contact:

«ያሬዳዊው» ኤልያስ መልካ

Unread post by selam sew »

«ያሬዳዊው» ኤልያስ ―
የዛሬ 15 ዓመት ገደማ የካቲት 19 ቀን 2001 ዓ·ም በጋዜጠኛ ማስረሻ ማሞ የተዘጋጀ ስለ ኤልያስ መልካ የሙዚቃ ሕይወት የሚያትት ጽሑፍ አዲስ ነገር ጋዜጣ ይዛ መውጣቷ የሚታወስ ሲሆን … የህልፈቱን 4ተኛ ዓመት ለማሰብ ያህል በሁለት ክፍል እንካችሁ! አንብቡት።
ጋዜጠኛ ማስረሻ ማሞ ከገነት ቤተ―ክርስቲያን እስከ በገና ስቱዲዮ ያደረገውን የኤልያስ መልካን የሙዚቃ ዱካ እንደሚከተለው ከትቦልናል፡፡

Image



፤፨፠፨፤ ― ክፍል አንድ ― ፤፨፠፨፤
የዛሬ ሦስት ዓመት ግድም (1998 ዓ·ም አካባቢ መሆኑ ነው።) ወደ ሃና ማርያም አካባቢ ለነበረው ቀጠሮ አክብሮ ለመገኘት የቅርብ ወዳጁ የኾነውን ዘካርያስ ጌታሁንን ከኋላ እና ከፊት ለፊት እዩኤል ሆሳዕና የሚባለውን ጓደኛውን አስቀምጦ ከቀኑአምስት ስዓት ሲኾን በቀለበት መንገድ ላይ በከፍተኛ ፍጥነት ይጋልብበታል፡፡ ኤልያስ ራሱን ጥንቃቄ እንደሚጎድለው ሾፌር ዐይቶትም አስቦትም አያውቅም። በዚያ ፍጥነት በሚበርበት አጋጣሚ ከፊት ለፊቱ የነበረው የዕቃ መጫኛ የሚጎትት አሽከርካሪ እርሱ የሚጓዝበትን አቅጣጫ ዘጋበት፣ ኤልያስ ከአደጋ ማምለጥ የሚችልበት ስዓት ወደ መጨረሻው ሰከንዶች ተቃርቧል፡፡
ሌላኛውን አቅጣጫ መምረጥ የመገልበጥን አደጋ ያመጣል፡፡ እኔም ኾንኹ ኤልያስ እንደምንጋጭ አውቀነዋል። እኔ ከኋላ ወንበር ላይ ኾኜ በጭንቀት የምይዘውም ኾነ የምጨብጠው አልነበረኝም:: ፊት ለፊት መኪናው ከዕቃ መጫኛው ጋራ ሊጋጭ ኮፈኑ መስተዋቱ ጋራ ደረሰ፡፡ ወንበሩ መትቶኝ የግራ እጄ መሰበሩን ያወቅኹት ከቆይታ በኋላ ነበር እንደ አጋጣሚ ኾኖ ኤልያስም ኾነ እዩኤል ምንም ዐይነት አደጋ አላገኛቸውም።» ይላል ዘካርያስ፣ ኤልያስ ከሞት ጋራ ፊት ለፊት መነጋገር ማለት ምን ማለት እንደኾነ የገባው በዚያች ቅጽበት በፈጠረቻት የሰከንድ ስሕተት አማካኝነት ነበር። ሹፌርነት ለኤልያስ ውኃ ከመጠጣትም የሚቀል ይመስለው ነበር። በአዲስ አበባ መንገዶች ላይ መኪና መንዳት ግን ውኃ እነደመጠጣት የሚቀል አልነበረም። በሰከንድ ውስጥ ሕይወትን ለመቀማት የሚያስችል ጉልበት ያለው እንጂ ለኤልያስ ይህ አጋጣሚ ሕይወትን ቆም ብሎ እንዲያስባት የሚያስገድድ ነበር፡፡ ያኔ ኤልያስ «አትቸኩል ረጋ ብለህ» የሚለውን ዘፈን ሊያደምጠውም ኾነ ሊያቀናብረው በሚችል መንገድ ገና አልታሰበም፡፡
ችኩልነትን ይተው ዘንድ ራሱንም ሌሎችንም የሚመክርበትን የመንገድ ትራንስፖርት ዘፈን ዝማሬ ከማቀናበሩ በፊት ኤልያስ ረጅም ጉዞ እና ጎዳና ተጉዞ ቦሌ መድኃኒዓለም ቤተ ክርስቲያን አካባቢ ካለው ስቱዲዮው ውስጥ ከተመ፣ ከካልዲስ ካፌ ፊት ለፊት በሬድዋን ሕንጻ ውስጥ ዘወትር ምሽት መብራቷ የማይጠፋው የኤልያስ ስቱዲዮ ናት፡፡
የክፍል ቁጥሯ 102 የኾነችው ይቺው ስቱዲዮ በዓለም አቀፍ ደረጃ ከሚታወቁት የሙዚቃ ሪከርዲንግ ስቱዲዮዎች አንፃር ስትታይ የስቴዲዮን ስፋት ያሟላች አይደለችም:: ጠባቧ ባለ ሁለት ክፍል ስቱዲዮ ከአምስት ሰው በላይ ሲገባባት በጭንቅ ትወጠራለች። ይኹን እንጂ እረፍት የለሽነቷ እንደ የጥበቷን ያህልም አይደለም። ምናልባትም ሌት እና ቀን መምሽት እና መንጋታቸው ሳይታወቅ አንዱ በሌላኛው ላይ እርስ በርሳቸው ይተካኩባታል፡፡ በዚች ጠባብ ስቱዲዮ ውስጥ የኢትዮጵያን ሙዚቃዎች የሚቀምረው ኤልያስ መልካ ከመሸገ ከርሟል፡፡ ስቱዲዮዋ ምንም እንኳ የምሽግነት ሚና ቢኖራትም ያለ ስያሜ የተፈጠረች አይደለችም፡፡ ጥንታዊውን እና የኢትዮጵያ የሙዚቃ መሣሪያ የኾነውን የበገናን ስም ወርሳለች፡፡
፤፨፠፨፤ ― በሙዚቃ ፍቅር ውስጥ የተገኘ ማንነት ― ፤፨፠፨፤
ኤልያስ መልካ የመሸገባት በገና ስቱዲዮ እንዲህ መፈናፈኛ ያጣች እስክትመስል ድረስ የጠበበቸው ለብቸኛው አቀናባሪ የምትበቃ በመኾኗ ብቻ አይመስልም፡፡ ሌላም የሚፈታ ምስጢር የምትገልጥ ትመስላለች፡፡ ከኤልያስ የሙዚቃ ሥራ እና የሕይወት ፍልስፍና ጋራ የሚጣጣም ዐይነት ትሥሥርን ሳታመላክትም አትቀርም። ኤልያስ በሙዚቃ ሥራ እና በጊታር ፍቅር ውስጥ ራሱን ካገኘበት ሰዓት አንስቶ ስለ ሙዚቃ አንድ ወጥ የኾነ መረዳት እና ግንዛቤ አልነበረውም፡፡ ራሱን በተለያዩ ውጣ ውረዶች ውስጥ አግኝቶታል፡፡ ያመነበትን ሲያደርግ፤ ያንን አመንኹበት ያለውንም ደግሞ በሌላ ዐይነት አዲስ ሓሳብ እና የሙዚቃ ግኝት ሊተካ እና ሲያፈራረቅ ከርሟል፡፡ በሕይወቱ ውስጥ ይህ ዐይነቱ መዘበራረቅ ሲገለባበጥ ተመልክቷል፡፡ ኤልያስ ውጣ ውረዱን እና በሕይወቱ ውስጥ ያለፈውን ዝብርቅርቅ ዓለም እንደ ሰፊ የሕይወት ተራራ ምዕራፍ ማየት አልመረጠም፡፡ ከዚያ ውስጥ ጥበብ ልታሰኝ ከምትችለው ትሩፋት ይልቅ ወደ አንድ አቅጣጫ ብቻ የዘንበለ እና ወይ አንድ ክፍል ብቻ እየጠበበ የሚሄድን ትርጓሜ መምረጥ የሚያዋጣ እና «ሰላም የሚሰጥ ነው።» ሲል አውጇል።
ነገሮችን ከመጽሐፍ ቅዱስ አውድ እና ትርጓሜ አንጻር መመልከት እና «እግዚብሔርን መፍራት የጥበብ ኹሉ መጀመሪያ ነው» በሚለው ላይ መንተራስ ለኤልያስ የሕይወት እና የሙዚቃ ሥራ ቁልፍ ጉዳይ ተደርገው ተወስደዋል፡፡
ኤልያስ አሁን ካለበት ድምዳሜ ላይ ከመድረሱ በፊት ባለፉት ዐሥር ዓመታት ውስጥ በብዙ መቶ የሚቆጠሩ ዘፈኖችን እና የፕሮቴስታንት መዝሙሮችን አቀናብሯል፡፡ መዝሙሮቹንም ኾነ ዘፈኖቹን ያቀናበረበት መንገድ የራሱ የኾነ አንድ ዐይነት ፍስት አልነበረውም፡፡ በተለያየ ጊዜ የተለያዩ ዐይነት የቅንብር ስታይሎችን ተጠቅሟል፡፡ ይህን የመቀያየር ስልት አንዳንድ የሙዚቃ ባለሞያዎች በየጊዜው ዕድገት እያሳየ ከመኾኑ ጋራ ያያይዙታል፡፡ የ23 ዓመት ልጅ ያቀናበረውን የቴዲ አፍሮን ሙዚቃ ስለማ እና በአዲስ አድማስ ጋዜጣ ላይ ስሜ ኣልተጠቀሰም ተጠቅሷል» በሚል ክርክር ኤልያስን ለመጀመሪያ ጊዜ ላወቀው የተፈጠረብኝ ስሜት የተለየ ነበር» ይላል የሙዚቃ ባለሞያው ሠርፀ ፍሬ ስብሐት፣ ሠርፀ ምን ምድር አፈራቸው ሲልም ኤልያስን እስቦታል፡፡

AddisDaily YouTube
Subscribe Our YouTube Channel




፤፨፠፨፤ ― የኤልያስ ጎሕ ሲቀድ ― ፤፨፠፨፤
ይህን የሙዚቃ ሰው ያፈራችው መንደር አዲስ አበባ ውስጥ ካሉት መንደሮች ኹሉ እጅግ ዝቅተኛ በሚባለው ረባዳ ስፍራ ውስጥ ትግኛለች፡፡ አዲስ አበባ ዳሎል የሚባል ስፍራ ሊሰየምላት ካስፈለገም ይቺን መንደር ሊቀድም - የሚችል አይኖርም። ከአብነት ወደ ሰባተኛ በሚወስደው መንገደ ላይ ከብሌን ሆቴል ፊት ለፊት ያለችው ይቺው መንደር እንደ ልብ ተንሰራፍተው የሚገቡባት አይደለችም፡፡ ወደ መንደሯ የሚያስገባው ቀጭን የአስፋልት መንገድ ሰዎች እና መኪናዎች እርስ በርሳቸው ያለመተፋፈር የሚገፋፉበት ነው፡፡
እርስ በርሳቸው የተዛዘሉ ትናንሽ ቤቶች ዳር እና ዳሩን አካባቢው እንዳይፈናፈን አድርገው ወጥረው ይዘውታል፡፡ ኤልያስ በዚያ ረባዳ ስፍራ ከዋናው መንገድ 300 ሜትር ያህል ወደ ውስጥ ዘልቆ በሚገኝ በግንብ በታጠረ ግቢ ውስጥ ነው ያደገው፡፡ ቤተሰቦቹ ፊደል እንዲቆጥር ወደ ትምህርት ቤት የላኩት የአራት ዓመት ልጅ ሳለ ነበር፡፡ ፊደል ከሚቆጥርበት ቦታ ሲመለስ ግን እንደ ልጆች በጋራ የሚያሳትፍን ጨዋታ ከማዘውተር ይልቅ በራሱ የጨዋታ ምርጫ መመሰጥን ይወድ ነበር:: ከቆርቆሮ የተሠሩ ቅራቅንቦዎችን ሰብስቦ እርስ በርላቸው እያጋጨ የሚያወጡት ድምጽ ይደሰት ነበር ይላሉ ወላጅ አባቱ አቶ መልካ ገረሱ፡፡ ኤልያስ ግን ይህን እንደሚያደርግ ትዝታው የለውም፡፡
ለኤልያስ ሙዚቃ በሕሊናው ታትሞ የቀረው በቤታቸው ውስጥ ይደረግ በነበረው የኅብረ ዝማሬ አጋጣሚ ነበር፡፡ የኤልያስ ቤተሰቦች የገነት ቤተክርስቲያን አባላት እና የፕሮቴስታንት እምነት ተከታዮች ናቸው፡፡ ደርግ የፕሮቴስታንት እምነት ተከታዮች ላይ ያደርግ በነበረው ተጽዕኖ ምክንያት የኤልያስ ቤተሰቦች እና መሰሎቻቸው በነፃነት የማምለክ ዕድል አልነበራቸውም፡፡ የራሳቸውንም ቤተክርስቲያን በአደባባይ ገንብቶ እንደፈለጉ የመኾን አጋጣሚ ጠባብ ነበር ያላቸው አማራጭ ሰፋ ያሉ ቤቶችን በድብቅ ለጸሎት' ለአምልኮ እና ለዝማሬ መጠቀም ነበር፡፡
ይህን ዐይነት አገልግሎት በመስጠት የእነ ኤልያስ ቤት በአካባቢው ቀዳሚ ስፍራ ያለው ነበር፡፡ ትንሹ ኤልያስ ከጸሎትም ከዝማሬም ከመጽሐፍ ቅዱስ ትምኅርትም በላይ ቀልቡ የሚወሰደው በጊታር ድምጽ ነው፡፡ ዘውትር ያለማቋረጥ የሚጫወተውን የገነት ቤተ ክርስቲያን ጊታር ተጫዋች የኾነውን ክፍሉ ወልዴን እንደ ጅል ፈዞ ያየዋል፡፡ ወዲያውም እርሱን በኾንሁ የሚለው ፍላጎት በልጅ ልቡ ውስጥ ይገላበጥበታል፡፡ ኤልያስ ግን በምኞት እና በፍላጎት ብቻ መታጠርን አልወደደውም፣ የፕሮግራም እረፍት እና የምሳ ሰዓት አጋጣሚን ተጠቅሞ የጊታሩን ክሮች በጣቱ እየነካካ ጣቶቹ በፈጠሩለት ድምጽ ይቦርቃል። ይህን ስሜቱን እና ፍላጎቱን የተረዱት አቶ መልካ ገረሱም ለኤልያስ ትናንሽ ጊታር መሰል ነገሮች እና ማሲንቆዎች ገዝተው ያመጡለታል፡፡ እህቶቹም የሙዚቃ መሣሪያ ስጦታ ያበረከቱለት ነበር ይላሉ አቶ መልካ
ጊታሪስቱ ክፍሎም የኤልያስን ፍላጎት ካወቀበት ጊዜ ጀምሮ ጊታር እንዲነካካ - በመፍቀድ ጊታር ፍቅር እንዲያድርበት አደረገው:: ለምጠይቀው ጥያቄ ኹሉ ላይሰለቹ አጠር ያለ መልስ ይሰጠኝ ነበር ይላል ኤልያስ፡፡ በ19 83 ዓ·ም ኢሕአዴግ አገሪቱን ሊቆጣጠር ኤልያስ የስምንተኛ ክፍል ተማሪ ነበር፡፡ ቤተሰቦቹ ለዕድገቱ እና ለችሎታው የሚመጥን የራሺያ ጊታር የገዙላትም ያኔ ነበር። ጊታሯን ግን ለራሱ ደስታ ብቻ ሊያደርጋት የሚችል አልነበረችም፡፡
በአካባቢው ያሉ የገነት ቤተ ክርስቲያን ኣባላት ፕሮግራሞች ላይ ዝማሬዎችን ማጀብ ዋነኛ ሥራው ኾነ፡፡ ኤልያስ ዝማሬዎቹን ከጀርባ ኾኖ ያጅብ እንጂ ዜማዎቹን መከተል እና ቀጥሎ የሚመጣው ዜማ ምን አንደኾነ የሚያውቅበት አንዳችም ችሎታ አልነበረውም፡፡ የመጀመሪያውን ዜማ ሳይጨርሱ ቀጥሎ ምን ሊመጣ ይችላል የሚለውን መገመትን የተማርኹት ያኔ ነው፤ አሁን በሥራዬ ላይም ጠቅሞኛል ይላል ኤልያስ።

Image

፤፨፠፨፤ ― በነዳጅ ማደያ የተለኮሰ ተሰጥኦ ― ፤፨፠፨፤
ኤልያስ በአንድ አጋጣሚ ከአማኑኤል አጂፕ ጋዝ ገዝቶ እንዲመጣ ቤተሰቦቹ ይልኩታል፥ የጋዝ ጀሪካኑን አንጠልጥሉ ከጋዝ ማደያው ጋራ ሲደርስ ወረፋው ብዙ ነበር:: ተራው ደርሶ ከኢሉ ብር ሲያወጣ እንድ ነገር ትወድቅበታለች:: የጋዝ ቀላው የወደቀችውን ነገር ዐይቶ ምን እንደኾነች ጠበቅ ባለ መንገድ ይጠይቀዋል፡፡ ትንሹ ኤልያስ ለሰውየው ጥያቄ አጭር እና ፈጣን ምላሽ ሰጠ፣ ፒክ ዋ ሲል፣ በኤልያስ ፈጣን ምላሽ የተገረመው ይኼ ሰው ልጁን ከእነ ጋዝ ወደ ቤቱ መላክን አልመረጠም።
ጊታር መጫወት ይችል እንደኾነ ከጠየቀው በኋላ ሊፈትነው ወደ ቢሮው ውስጥ አስገባው። ኤልያስ ወደ ቢሮው ከመግባቱ በፊት አንድ ወሳኝ ድርድር ተደራድሯል። ካልቻለ ኩርኩም ሊቀምስ፣ ኤልያስን ወደ ቢሮ ይዞት የገባው ሰው አቶ መለስ ይባላል። ኤልያስ ከአቶ መለስ ቢሮ ያገኛት ጊታር አንፈ እርሱ የራሺያ ጊታር ከባድ አይደለም። ለአጨዋወትም ኾነ ለአያያዝ የቀለለች ነበረች ቅለቷ ኤልያስ የበለጠ እንዲዝናና አደረገችው:: አቶ መለስ እና ኤልያስ የልብ ወዳጆች ኾኑ።
አቶ መለስ ኤልያስ ጋዝ ከመግዛትም ባሻገር ጊታርዋን እንዲጫወትባት ፈቀደለት ስለ ጊታር አጨዋወትም እነማን የተሻለ እንደኾኑ ያስረዳው ጀመር። በጊዜው የሮሃ ባንድ ጊታሪስት የነበረውን የሰላም ስዩምን በሙዚቃ መሣሪያ የተቀነባበሩ ሥራዎች እንዲያደምጥ ካሴት አዋሰው፡፡ ኤልያስ ሰላም ስዩምን በኅብረ ትርኢት በሚተላለፍ ክሊፕ ላይ ከማየት ባለፈ ማን እንደኾነ እንኳ አያውቅም ነበር:: ኹሌም ኅብረ ትርኢት ላይ ሲጫወት ሳየው ግን በጣም እገረም ነበር። ይላል፡፡ የአቶ መለስ የሰላም ስዩም ወሬ ኤልያስን ስለ ስዩም ከማሳወቅም አልፎ የሥራው ተከታይ እንዲኾንም አደረገው፡፡ «እንደ ሰላም ለመጫወት የኅብረ ትርኢቱን ለማስመሰል (Imitate) ጥረት አደርግ ነበር። ይላል ኢልያስ።
ኤልያስ በአካባቢው የነበረውን የገነት ቤተ ክርስቲያን ኅብረት የሴቶች፣ የወጣቶች እና የቤተሰብ ፕሮግራም ሳያቋርጡ መጫወት አንዳንድ ጊዜ መሰልቸትን እና ድካምን ይፈጥርበት እንደነበር ያወሳል። በዚያው ወቅት ኤልያስ ለቤተ ክርስቲያን ዝማሬ ከኳየር ጋራ ተቀላቀለ፡፡ ኳየሩ የእናቱ እኩዮች የሚዘምሩበት ነበር፡፡ ቤተክርስቲያን ከጊታርም ባለፈ ከሌሎች የሙዚቃ መሣሪያዎች ጋራ እንዲተዋወቅ ዕድል ፈጠረችለት:: ፒያኖ እና በዐይነታቸው ልዩ የኾኑ ጊታሮችን የማግኘት ዕድሉም ሰፊ ኾነለት፡፡ የኤልያስ ነፍስ የሙዚቃ ጥማቷን ለማርካት ከተማዋ ውስጥ አሉ የሚላቸውን የሙዚቃ ትምህርት ቤቶች እንዲያስስ አድርጎት ነበር፡፡
selam sew
Leader
Leader
Posts: 690
Joined: 08 Feb 2011 11:14
Contact:

Re: «ያሬዳዊው» ኤልያስ መልካ

Unread post by selam sew »

፤፨፠፨፤ ― ላለው ይጨመርለታል ― ፤፨፠፨፤
የፕሮቴስታንት መዝሙሮችን በማቀናበር የሚታወቀው ጌታ ያውቃል ግርማይ እውቅና ያለው እና የሚሠራቸው መዝሙሮች ተወዳጅነት ያተረፉ ናቸው፡፡ ኤልያስ ኹል ጊዜ የጌታ ያውቃልን ሥራዎች ማድመጥ አይሰለቸውም፡፡ እንዲያውም ጊታርን አብዝቶ ስለሚጠቀም ስሜቱን ይማርከዋል። ስለ ጌታ ያውቃል የሚያውቀውም ገና ልጅ ሳለ ነበር፡፡ የጌታ ያውቃል የሙዚቃ ትምህርት ቤት መክፈት ደግሞ ለኤልያስ የሕይወቱን ምዕራፍ አንድ ርምጃ ከፍ የሚያደርግለት ኾነ፡፡ ትምህርት ቤቱ ውስጥ ሊመዘገብ መጀመሪያ ያገኘው ጌታ ያውቃል ሳይኾን እያሱ ገነቴ የተባለውን መምህር ነበር። እያሱን አጣጥሞ ሳይጨርስ ጌታ ያውቃልን የማግኘት ዕድል ገጠመው። ጌታ ያውቃል በጊታር አጨዋወት ላይ ካለኝም ባላይ ጨመረልኝ። ይላል ኤልያስ ጌታ ያውቃልን የወጣላት የሙዚቃ ተጫዋች እንዲኾን ያደረጉት ወላጅ አባቱ ሻለቃ ግርማይ ሓድጎ ናቸው። ሻለቃ ግርማይ ከእነ ሳህሌ ደጋጎ፣ ከእነ ለማ ደምሰው እና ከእነ ኮሎኔል ኃይሉ ወልደ ማርያም ጋር የሚመደቡ አቀናባሪ እና የግጥም ደራሲ ናቸው። በወታደራዊ በኾነው የአሠለጣጠን ጠባያቸው ልጃቸውን ጌታ ያውቃልን እንደገሩት ደጋግሞ ሲናገር መስማቱን የዐሥራ አራት ዓመት ጓደኛው እና ሙዚቃን አብሮት የሚጫወተው ዘካርያስ ጌታሁን ይናገርለታል። ጌታ ያውቃል ሙዚቃ ሲያለማምድ አይቀልድም። የአባቱ ቀጥተኛ ተጽእኖ ተጋብቶበታል፡፡ ይህ ደግሞ እንደ ኤልያስ ላሉ ስጦታ ለተቸራቸው ሙዚቀኞች በየጊዜው መሥራትን ያተርፍላቸዋል ይላሉ በሙዚቃ ሥራ ውስጥ ያሉ ባለሞያዎች።
፤፨፠፨፤ ― ኤልያስም እንደ ቅዱስ ያሬድ ?? ― ፤፨፠፨፤
ኤልያስ የዐሥራ አንደኛ ክፍል ተማሪ እያለ ያሬድ የሙዚቃ ትምህርት ቤት ውስጥ መመዝገብ እንደሚቻል ይሰማል። ያሬድ ትምህርት ቤት ውስጥ ከ200 ያላነሱ ተማሪዎች ለምዝገባ ተኮልኩለዋል። ከልጅነቱ ጀምሮ ሙዚቃ ውስጥ ለነበረው ኤልያስ ያ ዕድል ሌላ የሕይወት ምዕራፍ የተከፈተበት ነበር፡፡ ከተፈተኑት ተማሪዎች መካከል ሰባተኛ ወጥቶ «ቼሎ» እንዲያጠና ተመደበ። ኤልያስ ያሬድ ትምህርት ቤት ውስጥ ስለ ሙዚቃ ትምህርት ቤቱ እና ስለ ሙዘቃ የተሰጠው ኦሬንቴሽን በሕይወቱ ውስጥ ተሰምቶት የማያውቅን ልዩ ደስታ ፈጠረለት። ወደ ትምህርት ቤት ሄጀ አንድም ቀን ደስተኝነት ተሰምቶኝ አላውቅም ነበር። እንዲያውም በትምህርት ሰነፍ ነበርኹ። ያን ጊዜ የተሰማኝ ስሜት ግን ወደር አልነበረውም። ይላል ኤልያስ የሕይወቱ ማለዳ (Defining Moment) የጀመረበትን ዘመን እያስታወሰ። በዚያ ኦረንቴሽን የሕይወቱ ማለዳ ሲጀመር በልቡ እንድ ነገር ወሰነ። ዳግም ወደ ከፍተኛ ሰባት ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ላይመለስ ቀሪዎቹን የዐሥራ ሁለተኛ ክፍል መልቀቂያ ስድስት የትምህርት ወራት በፍጹም ሊያያቸውም ኾነ ሊመለስባቸው አልፈለገም። እንደምንም ብሎ የገፋቸውን እነዚህን ዓመታት እንደ ቀልድ እንዲተዋቸው ያልፈለጉት እናቱ ወይዘሮ ጸዳለ ፈለቀ ግን የኤልያስ ሐሳብ መቀበል አልፈለጉም፡፡ ኹሉም ነገር ከማትሪክ በኋላ ይደርሳል ነበር ያለችኝ ይላል፤ አባቴም የተለመደውን ምክራቸውን ከመለገስ ውጭ በምርጫው እና በነፃ ፍላጎቱ ላይ ጣልቃ መግባት ስላልፈለጉ ለውሳኔው ተውት። «እንኳንስ ዕድሜው ለምርጫ ደርሶ ቀርቶ በሕፃንነቱም ቢኾን ፍላጎቱ ላይ ማንም ጣልቃ ገብተን አስቁሞት አያውቅም።» ይላሉ ለልጆቻችው ነፃነትን መስጠትን እንደ ትክክለኛ የሕይወት ፍልስፍና የወሰዱት የኤልያስ አባት አቶ መልካ ገረሱ።
፤፨፠፨፤ ― «ስጦታው ያለው ጊታሪስት እና አቀናባሪ» ― ፤፨፠፨፤
ኤልያስ የያሬድ ትምህርት ቤት ካፈራቻቸው ሙዚቀኞች ምርጡ እና አንዱ እንደኾነ የሚናገሩለት ባለሞያዎች ብዙ ናቸው። የሙዚቃ ባለሞያው እና የአዲስ ነገር የሙዚቃ አምድ ጸሐፊ ሠርፀ ፍሬ ስብሐት Sertse Firesbhat «ከሙሉጌታ አባተ በኋላ የቅንብርን ስታይል በተለየ መንገድ ያስተዋወቀ እና በአጨዋወት ሥልቱ ለሌሎችም አርአያ እና ምሳሌ መኾን የቻለ አቀናባሪ ነው።» ይለዋል። ኤልያስ በሥራውም ኾነ በትምህርቱ የተዋጣለት አና ስኬት ላይ ያለ ነው ሲሉ የሚያደምጡትም ቀላል ድምፅ የሚወክሉ አይደለም። የሚያውቁት በሙሉ በአንድ ድምፅ «ስጦታው ያለው ጊታሪስት እና አቀናባሪ» ሲሉ ያወድሱታል።
፤፨፠፨፤ ― የድምፁ መሐንዲስ ― ፤፨፠፨፤
ኤልያስ ከዓመት ወደ ዓመት ለውጥ እያሳየ እንደኾነም የሚመሰክሩለት ብዙ ናቸው፡፡ ለእንደ የተዋጣለት ሙዚቀኛ ከሚለካባቸው ነገሮች አንዱ እና ዋነኛው ነገር የማድመጥ ብቃት ነው። በሙዚቃ ሰፈር የሚመላለስ ሰው ጆሮ ሊኖረው ግድ ይላል ይላሉ ባለሞያዎቹ። «ከጆሮም በላይ ትልቅ ጆሮ አለው።» ይለዋል የመሐሪ ብራዘርስ ባንድ መሥራች እና ሥራ አስኪያጅ ሄኖክ መሓሪ። ኤልያስ ከጥሩ ሰሚነቱም ባሻገር የዘፋኞችን ድምፅ የሚገራ፣ ጆሮን የሚወጉ ድምፆችን ለማስወገድ ጥረት የሚያደርግ የታጨቁ ድምፆችን የሚጠላ ጩኸት ከበዛባቸው ድምፆች ይልቅ የተረጋጋ ድምፅ መስማት ላይ የሚያተኩር አና ዜማን የሚቆጥብ እና የሚመጥን ነው ሲልም ይገልጸዋል።
ሄኖክ ኤልያስን እንደ መልካም አባት እና መምህርም አድርጎ ነው የሚወስደው። ከድምፃውያን ጋር ያለው ቅርበት እና የአንዳንዶቹን ድምፃውያን ዘፈኖች መሉ ለሙሉ አፍርሶ ለመሥራት ያለው ትጋት በአብዛኞች አቀናባሪዎች ዘንድ ያልተለመደ እና የማይገኝ ነው ሲሉም ያሞካሹታል። ለኤልያስ ግን ይህ የዕለት ተዕለት ተግባሩ ነው፡፡ ቀን እና ሌትን የምታፈራርቅ ስቱዲዮው ለዚህ በቂ ምስክር መኾኗን በቅርቡ ያሉ ወደጆቹ የሚመሰክሩበት ጉዳይ ነው። ሠርፀ ለሮክ እና ለካንትሪ የቀረበ ድምጫ አለው የሚለውን ኤልያስን ዜማ አፍርሶ መሥራቱን «ከቅንነት የሚመነጭ፣ ሕላዌ መዝራት» ሲል ይገልፀዋል።
፤፨፠፨፤ ― በመዝሙር የተቀደሰው የቅንብር ጅማሮ ― ፤፨፠፨፤
ኤልያስ አሁን ወደ አለበት ኹኔታ ውስጥ ከመምጣቱ በፊት ለመጀመሪያ ጊዜ ማቀናበርን የተለማመደው በመዝሙር ነበር፡፡ ዝማሬዎችን ለማቀናበር የቤተ ክርስቲያን አገልግሎቱ በሩን ቀስ በቀስ አስፍቶለት ነበር።
በየመድረኩ ላይ ከጓደኞቹ ጋራ በሚያቀርቡት የመዝሙር ማጀብ ሥራ ታዋቂነትን ያገኙበት ዘመን ነበር። ጊዜው በያሬድ የሙዚቃ ትምህርት ቤት ውስጥ ሙዚቃ የሚጠናበት እና የጃዝ ሙዚቃዎች የሚደመጡበት ስለነበር ጠንካራ የኾኑ «ኮርዶችን» እያስገቡ መጫወትን እንደ ጀብድ እና ከበድ ያሉ ነገሮችን በመቀላቀል ሰዎችን ለማስደመም ጥረት የሚደረግበት እንደነበር ይገልጻል ኤልያስ።
ኤልያስ ለመጀመሪያ ጊዜ ሦስተኛውን የአገኘሁ ይደግን መዝሙር እንዲያቀናብር ሲጋበዝ ይህንኑ የመደነቅ እና የማስደመም ፍላጎት ተንተርሶ ቀላቅሎ በማቅረቡ በመዝሙሩ ላይ ተገቢ ያልኾነ የቅንብር ሥራ ማከናወኑን እስከዛሬም ይጸጸትበታል።
፤፨፠፨፤ ― በመዲና እና በኮንኮርድ ― ፤፨፠፨፤
ይኹን እንጂ ያንን ያደረገው ከቅንነት ማጣት ወይም ኾነ ብሎ ለማበላሸት አስቦ አልነበረም። «የወጣትነት እና የፍንዳታ ዘመን ስለነበረ ነው።» ይላል፡፡ በጊዜው ቤት ውስጥ የነበሩት ሰዎች እናቱን ጨምሮ መዝሙሩ አልዋጥላቸው ሲል መባነን እንደነበረበትም ያወሳል፡፡ ወቅቱ ስለ ኤልያስ የጊታር ችሎታ የሚጠራበት ስለ ነበር እርሱን እና ጓደኞቹን እና ዮሐንስ ጦናን ለማጫወት የሚፈልጉ ባንዶች ነበሩ። ኤልያስ ቀልጣፋ እና ራሱን መሸጥ የሚችል ዐይነት ሰው አልነበረም፡፡ ከአዋሳ የመጣው ዮሐንስ ጦና ግን ችሎታውን ለማሳየት እና ራስን ለማስተዋወቅ የማይፈራ ልጅ ነበር። ይላል ኢልያስ።
ኤልያስ የአራተኛ ዓመት ተማሪ እያለ ከመዲና ባንድ ጋራ የመጫወትን ዕድል አገኘ፣ አጨዋወታቸውን ያየው የመዲና ባንዱ እዝራ አባተ የባንዱ ሰዎች በማይኖሩበት አጋጣሚ እነ ኤልያስ እየተኩ እንዲሠሩ አደረጋቸው። በአንድ አጋጣሚ ትዕግሥት በቀለ መድረክ ላይ ስትጫወት የባንዱ ጊታሪስት አልተገኘም ነበር። ኤልያስ ያን አጋጣሚውን ተጠቀመበት። «ሙዚቃው የጃዝ ዐይነት አጨዋወት ስለነበረው ልምምድ ባላደርግም አብሮ በተለመደ አጨዋወት ለመጓዝ ያን ያህል አዳጋች አልኾነብኝም» ይላል ኤልያስ። ከዚያ በኋላ ኤልያስ ቀጥታ የተዛወረው መዲና ባንዶች ይሠሩበት ወደነበረው ኮንኮርድ ሆቴል ነበር፡፡ ትንሹ ልጅ ኤልያስ በተቀጠረበት ሰዓት የኮንኮርድን ናይት ክለብ በሮች አልፎ ለመግባት የሚያስችል ዕድሜ ላይ አልነበረም፡፡ ኻያ አምስት ዓመት ያልሞላው ሰው ወደ ውስጠኛው የናይት ክለብ ክፍል መግባት አይችልም፡፡ ኤልያስ በመዲና ባንዶች ዕገዛ ወደ ውስጥ ዘለቀ። ኤልያስ በዚያ ዐይነቱ ደብዛዛ ብርሃን ወስጥ የሚያያቸውን ትዕይንቶች ለማመን ተቸግሯል። ይህ ዐይነቱ ሕይወት ለእርሱ በጣም ሩቅ እና ሰምቶትም እንኳ የሚያውቀው አልነበረም፡፡ ለወጉ ያህል ጨርቅ ጣል የተደረገበት የሴት ገላ የወንዶች እቅፍ ውስጥ ኾነው መዚቃ እየሰሙ የሚውረገረጉ ጉብሎች ሲጋራ እንደ እጣን የሚትጎለጎለበት እና ሲጋራ ካልተጨሰ ቆሌው የማይታረቀው የሚመስለውን ምሽት መመልከት ለኤልያስ በሕልም እና በእውን መካከል እንደመቃዠት ነበር፡፡
፤፨፠፨፤ ― የኤልያስ የዕንቅፋት ደንጎች ― ፤፨፠፨፤
ቀስ በቀስ ግን ኤልያስ ለራሱ እንግዳ በነበረው የጨለማው ዓለም ውስጥ ዋነኛ ተዋናይ መኾን ጀመረ፡፡ «የባንዱ መሪ እዝራ ሙዚቃውን ከተጫወትን በኋላ በቀጥታ ወደ ቤታችን እንድሄድ ርምጃችንን ሳይቀር ለመቆጣጠር ጥረት ያደርጋል፡፡ ነገር ግን እኔ እየተደበቅኹ ማጨስ ጀመርኩ።» ይላል።
ለኤልያስ የጥፋት የሚባሉት ግመታት የተጀመሩት ያኔ ነበር፣ በመድረክ ላይ የሚወራው ሙዚቃ እና የሚያቀናብረውን መዝሙር ከኢትዮጵያ የዘፈን ሙዚቃ ጋራ እንዴት አድርጎ ማጣጣም እንዳለበት ማሰብም ጀምሮ ነበር። ለመጀመሪያ ጊዜ የመሐሙድ አሕመድን «ሁሉም ይስማ» እና አንድ የጉራጊኛ ዘፈን አቀናበረ፣ ከዚያ በኋላ የቴዲ አፍሮ - «አቡጊዳ»ን ሙሉ ካሴት ሠራ፣ ኤልያስ ከመድረክ አልፎ ወደ አደባባይ እና ወደ ሕዝብ ጆሮ ሲገባ «ያሳደግኹት ልጄ እና ንብረቴ ነው።» የሚለው የፕሮቴስታንት አማኞች ጥያቄ የሚዲያዎች ትልቁ የመወያያ ርዕስ ሆኖ ነበር፡፡
ከዚያም ባሻገር በቴዲ ሥራ ላይ ስሜ አልተጠቀሰም የሚለው ኤልያስ በአደባባይ የወቅቱ ዜና ኾኖም ነበር። የፕሮቴስታንት መጽሔቶች ኤልያስን ቃለ መጠይቅ እያደረጉ «ስለምን ወደ ዓለማዊ ሙዚቃ ገባህ?» እያለ ይሞግቱታል። ስለ ድካሙ የሚከፈለው የገንዘብ ጥያቄም የርእሰ ጉዳዩ አንዱ አካል ነበር፡፡ ኤልያስ ያን ጊዜ የሰጣቸውን አብዛኞቹን ቃለ ምልልሶች «ከጉርምስና እና ከጀብደኝነት ጋራ የተያያዘ» ሲል ይገልጻቸዋል፡፡ ያኔ ለሚነሱት ጥያቄዎች ሁሉ የመሰላቸውን መልስ መስጠትን እንደ ግዴታ የሚቆጥሩበት አጋጣሚ ትክክል አለመኾኑንም ያወሳል። «ገንዘብ ያስፈልገናል የሚል ጥያቄ አስቀድሜ ሳላነሳ የገንዘብ ችግር አለ ብዬ ቤተ ክርስቲያንን መውቀስ አግባብ አልነበረም።» ይላል፡፡
፤፨፠፨፤ ― ምዑዝ ኤልያስ ― ፤፨፠፨፤
ኤልያስ ሕይወቱን በሙዚቃ ቅንብር ባሳለፈባቸው ዓመታት ውስጥ የራሱ የኾኑ ዘመናት ነበሩት፡፡ የእነ መሐሙድ አሕመድ እና ቴዲ አፍሮ ዘመን፣ የእነ ጎሳዬ ተስፋዬ እና የእነ ይርዳው ጤናው ዘመን እንዲኹም የእነ አብነት አጎናፍር፤ የእነ ዘሪቱ ከበደ እና የእነ ኢዮብ ዘመን ብለን ልንከፍላቸው እንችላለን ይላል ሰርፀ፡፡ ለኤልያስም እነዚህ የዘመን ክፍፍሎች ይስማሙታል ዘፈኖቹን ወደ ኋላ ተመልሶ ባደመጣቸው ቁጥር የቅንብራቸው መዓዛ ዜማዎቹን የሠራባቸውን ዘመናት ያስታውሱታል። ለዜማ ትኩረት የሚሰጥባቸው ጊዜያት ነበሩት:: የትኛውንም ግጥም ከዜማው ጋራ እንዴት አድርጎ ሊያሰናስለው እንደሚችል ብቻ ያስባል፡፡ ዘፋኞቹም የመጣውን መልእክት ሳይነካባቸው ማስተላለፍ ይሻሉ፡፡ ዜማን በቅንብር ክሂሉ የሚያጣፍጠው ምዑዝ ኤልያስ ዜማውን የሚያደናቅፍ ነገር እስካልገጠመው ድረስ የግጥሞቹ ይዘት እና መልእክት ያን ያህል አያስጨንቀውም ነበር፣ አሁን ግን እንደዚያ ማሰቡን እቁሟል፣ በፈን ውስጥ የሚተላለፉ መልእክቶች የአድማጭን ብሶት የሚያጠናክሩ ያዘነውን የሚያስለቅስ፤ መለያየትን የሚያበረታቱ እና ዝሙትን እና ኃጢያትን የሚያሞካሹ መኾን የለባቸውም የሚል አቋም ላይ ደርሷል፡፡ ከዚህ መለኪያ ፈቀቅ የሚል ካለም ሌላ አቀናባሪ እንዲሠራለት ይልከዋል እንጂ በዚህ ላይ መደራደርን አይመርጥም፡፡ «ይህ አቋም ኤልያስ ከአቀናባሪነት ወደ ፕሮዲዩሰርነት ራሱን ያሸጋገረበት ነው።» ይላሉ የሙዚቃ ባለሞያዎቹ። «ራሱ ፕሮዲዩስ ያደረጋቸው የኢዮብ እና የዘሪቱ ሥራዎች ስኬታማ ሆነውለታል።» ይላል ሰርፀ።የኤልያስ ወደ ፕሮዲውሰርነት ማደግ ከዜመኝነትም ባሻገር ወደ ገጣሚነት ከፍ ከማለቱ ጋራ ይያያዛል። የኢዮብን ዐሥሩን ሥራዎች በግጥምም በዜማም የሠራው እርሱ ነው። የግጥሞቹ አብዛኞቹ ቃላት እና የመልእክት ይዘታቸው መጽሐፍ ቅዱሳዊ ነው። ያ ቀጥተኛ ተጽእኖ በኤልያስ ላይ የታየው ለማንበብ የሚመርጠው ብቸኛ መጽሐፍ ቅዱስ መጽሐፍ ስለኾነ ነው። አንዳንዶች ይህ ምርጫው «ዘፈኖችን በዘፈን እና በመዝሙር መካከል የሚዋልሉ» እንዲኾኑ አድርጓቸዋል ብለው ያምናሉ።
፤፨፠፨፤ ― ኹሉን የማያነብ ሙዚቀኛ ― ፤፨፠፨፤
ኤልያስ ወደ ስቱዲዮ ባልገባባቸው በእነዚያ ዓመታት የእነ ስብሐት እና በአማርኛ የሚጻፉ ፍልስፍናዎች አድናቂ እና አንባቢ ነበር፡፡ ስለ ፖለቲካ፤ ስለ ማኅበራዊ ጉዳይ፥ ስለ ፍቅር ግንኙነት እና ስለ አገርም ኾነ ዓለም ጉዳይ የሚዳስሱ ጽሑፎችን እያነበቡ መከራከር እና መጠያየቅ የእንድ ወቅት ልማዱ አድርጎት ነበር። «ይኹን እንጂ ትልቅ ሰው ጻፈው የተባለውን መጽሐፍ በአጭሩ መጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ማግኘት ይቻላል።» የሚለው ሐሳብ ሞያውን ከሚመለከት ጉዳይ ውጭ ሌላ መጻሕፍት ያለማንበብን ዝንባሌን አሳድሮበታል። ይህን አካሄዱን አንዳንድ ሰዎች «የነገሮችን ስፋት እና ጥልቀት ከአንድ አቅጣጫ ብቻ በማየት እና በመተርጎም ጥበብን በአንድ ጎን ብቻ የተሰፋች አድርጎ መመልከት ጥበብን ራሷን ማጥበብ ይኾናል።» ሲሉ ይተቹታል። የኤልያስ ግጥሞች ሥነ ምግባራዊነትን የሚሰብኩ ናቸው። በማጽናናት እና በተስፋ ማድረግ ላይ የተመሠረቱ ናቸው። ስለ ውበት፣ ስለ ፍቅር፤ በሌላው ላይ ስለመፍረድ እና በቋንቋ ብቻ መፈላሰፍ ምን ጠቀሜታ አለው የሚሉ ሐሳቦችን ይዳስሳል። ኤልያስ በጠባቧ ስቱዲዮው ውስጥ የአንዳንድ ዘፋኞችን ግጥም እንዲህ ቢኾንስ እያለ የአርትኦት ሥራ ይሠራል። አንዳንዴም ከዜሮ አንስቶ ለዘፈንነት የሚያበቃቸው እንዳሉ እንደ ሄኖክ መሐሪ ያሉ የሥራ ባልደረቦቹ ይናገሩለታል። ይመሰክሩለታልሁ።
፤፨፠፨፤ ― በጥያቄ ውስጥ ያለ «ሞራሊስት» ― ፤፨፠፨፤
ኤልያስ በእነዚህ ጉዞዎቹ የደረሰው ሞራሊስት ሙዚቀኛ ወደሚለው መጠሪያ ነው። የሚሉ ባለሞያዎችም አሉ፣ ግጥሞች «እግዚአብሔርን ከመፍራት ጥበብ እና እርሱን ያስከፉታል።» ብሎ ከሚያስባቸው ነገሮች ጋራ የሚጋጩ መስሎ ከታየው ወደ ዘፈንነት አይቀይራቸውም። ለዜማ ሊበቁ ይገባል የሚል እምነትም የለውም። ይኹን እንጂ ኤልያስ ከመሸገበት ስቱዲዮ ውስጥ የኢትዮጵያውያንን ጆሮ የሚያረሰርሱ ሙዚቃዎች ታሽተው እና ተቀምረው የሚወጡት መቶ በመቶ ኢትዮጵያውያን የሥነ ምግባር መለኪያ አድርገው ካስቀመጧቸው ሱሰኝነት ጋራ ሳይጋቡ ቀርተው አይደለም። ከመኪና አደጋው በኋላ ከመጠጥ ጋራ የተሰናበተው ኤልያስ እነዚሁኑ ሙዚቃዎች ሲሰፋ እና ሲጠግን አብዛኛውን ጊዜውንም የሚያጠፋው በስቱዲዮ ውስጥ ነው። ስቱዲዮው ግን ከጫት እና ከሲጋራው ሊያስጥለው አልቻለም። «ሲጋራ ለማቆም ሞከርኽ ነገር ግን አልቻልሁም። ጫት ላቁም ብዬ ግን አስቤ አላውቅም። ሁለቱንም የማቆም ፍላጎት አለኝ።» ይላል። ኤልያስ ይህን ከመሰለው መተው አለመተው ጉዳይ ጋራ ቢጋፈጥም በዘፈኖቹ ሊያሳይ የሚፈልገውን ሥነ ምግባራዊነት በተግባር በራሱ ላይ ሙሉ ለሙሉ ማሳየት አልቻለም ሲሉ መልሰው የሥነ ምግባራዊነት ጥያቄ የሚያነሱም አሉ፡፡
ከዚህም በተጨማሪ ጥበብ ሰፊውን ባህር ለመቅዘፍ ካላት ዕድል አንፃር በራሷ ሰፊ የኾነች ናት። ፍልስፍና፤ ሳይንስ፣ ሐይማኖት፣ ፖለቲካ፣ ማኅበራዊ ሕይወት፣ የጥላቻ እና የሰላም አየሮች በፍልቀት የሚነፍስባትም ናት። ብለው የሚያስቧትም በሕፃንነት በጊታር ፍቅር በተለከፈው የኤልያስ ዓለም ሥነ ምግባር ብቻ ሆና አልጠበበችም ወይ? የሚል ጥያቄ ያነሳሉ። ጥበብ እንደ ስቱዲዮው እየጠበበች እና እየተተረጎመች ወይስ ወደ መጽሐፍ ቅዱስ ባህር ውስጥ ገብታ እየሰፋች? ይላሉ። ኤልያስ ብር የማግኘት አጋጣሚው ሰፊ በኾነለት በዚያ ዘመን የአስቴር አወቀን ኮንሰርት መሥራትን ጨምሮ በማቀናበር ባገኘው ብር መኪና ገዝቶ ነበር፡፡ ያለ ልክ መጠጣትንም ያዘወተረው ያኔ ነበር። ሲጋራ ማጨስን እና እንደ ጌጥ ማንቦልቦልንም እንዲኹ፡፡ ኤልያስ በሲጋራ እና በግብረ አበሮቹ ላይ አጅግ በርትቶባቸው ነበር። በግል ሕይወቱ እና በዙሪያው ባሉ ሰዎች ላይ ያደረሰውን ጉዳት ግን አስደንግጦታል። የመኪና አደጋ በብር ያወጣውን መንጃ ፈቃድ ሳይቀር ለመንገድ ትራንስፖርት እንዲመልስ አስወስኖበታል። ይህን ለማድረግ ያስቻለው ለራስ ታማኝ የመኾን ጉዳይ የጀመረውን የሥነ ምግባራዊነት ጉዞ እስከ መጨረሻው ያስቀጥለው ይኾን?
በሚል ጥያቄ ጋዜጠኛው ማስረሻ ማሞ ለጋዜጣው ያዘጋጀውን ጽሑፍ አጠቃልሎታል።
፧፠፨፠፧ ― ነብስህ በሰላም ትረፍ! ኤላ ― ፧፠፨፠፧
፧፠፨፠፧ ― MULER Design & Art ― Photographer MULER ― ፧፠፨፠፧

Via: Facebook Muluken Asrat: https://www.facebook.com/mulukenasrat
selam sew
Leader
Leader
Posts: 690
Joined: 08 Feb 2011 11:14
Contact:

Re: «ያሬዳዊው» ኤልያስ መልካ

Unread post by selam sew »

Best of Elias Melka Songs የኤልያስ መልካ ምርጥ የሙዚቃ ስራዎች

AddisDaily YouTube
Subscribe Our YouTube Channel


selam sew
Leader
Leader
Posts: 690
Joined: 08 Feb 2011 11:14
Contact:

Re: «ያሬዳዊው» ኤልያስ መልካ

Unread post by selam sew »

የኤልያስ መልካ የ 90 ዎቹ ምርጥ የፋቅር ዘፈኖች ስብስብ Eliase Melka 90s music old Ethiopian music 90s Ethiopian music

AddisDaily YouTube
Subscribe Our YouTube Channel


Post Reply

Return to “Ethio Art and Culture..ኢትዮ ጥበብ ፤ስነ ጽሁፍ ፤”