ለቸኮለ! የዛሬ ሐሙስ ሐምሌ 26/2010 አበይት ዜናዎች - Wazema Radio
1. በዛሬው ዕለት በተቀሰቀሰ ኹከት በኮምቦልቻና ደሴ መሐል ያለው መንገድ ተዘግቷል፡፡ ስለጉዳዩ ዝርዝር መረጃ እያፈላለግን ነው
2. የኦሮሞ ድርጅቶች ወደ አንድነት እንዲመጡ እንቅስቃሴ መጀመሩን የገለጹት “የኦሮሞ ዴሞክራሲያዊ ግንባር” (ኦዴግ) አመራር ዲማ ኖጎ (ዶ/ር) ከተቃዋሚ ፓርቲ ብቻ ሳይሆን ሥልጣን ላይ ካለ የኦሮሞ ድርጅት ጋር እንደሚነጋገሩ ጠቅሰው “ተመሳሳይ አቋም ካለን ሥልጣን ላይ ካለው ጋርም የማንተባበርበት ምክንያት የለም” ብለዋል፡፡ ፓርቲዎች ሲደራጁ ዓላማ አስቀምጠው፣ ሕዝባዊ መሰረት ይዘው ሳይሆን… ተደብቆ በሕቡዕ ወይም በትጥቅ ትግል እንደነበር ያስታወሱት ዲማ ኖጎ “ይሕ መሆኑ ፓርቲዎችን የጠባብ ቡድን ስሜት ሠለባ አድርጓቸዋል” ሲሉ ተናግረዋል፡፡ በአሁኑ ወቅት በኦሮሞ ሕዝብ ስም ከ13 በላይ ፖለቲካ ፓርቲዎች በመንቀሳቀስ ላይ ይገኛሉ፡፡
3. እየተጠናቀቀ ባለው የሐምሌ ወር የዋጋ ግሽበት 14 % መሆኑን ከማዕከላዊ ስታቲስቲክስ ባለሥልጣን የተገኘው መረጃ ያመለክታል፡፡ ከሰኔ ወር ጋር ሲነጻጸር በእሕል፣ አትክልትና ፍራፍሬ እንዲሁም ቅመማ ቅመም ላይ ጭማሪ ተመዝግቧል፡፡ ምግብ ነክ ባልሆኑ ሸቀጦች ላይም ግሽበቱ ከፍ ብሏል፡፡ የምግብ ዋጋ ግሽበት 16.7 % ሆኖ ሲመዘገብ፣ ምግብ ነክ ያልሆኑ ሸቀጦች ግሽበት 10.9 % ደርሷል፡፡
4. በመስከረም 2011 ዓ.ም በተባበሩት መንግስታት ድርጅት ጠቅላላ ጉባዔ በሚካሄደው የታዋቂ ሰዎች ክርክር ላይ ጠ/ሚ ዐብይ አሕመድ ተናጋሪ ሆነው መጋበዝ እንደሚገባቸው ተጠቆመ፡፡ መስከረም 7/2011 ዓ.ም በኒውዮርክ 74ኛ ጉባዔ በሚካሄደው የክርክርና ውይይት ፕሮግራም ዐብይ አሕመድ እንዲጋበዙ የጠቆሙት በመንግስታቱ ድርጅት የስዊድን አምባሳደር ኦሎፍ ስኮግ ናቸው፡፡ ዓለም አቀፉ ማሕበረሰብ ላለፉት 20 ዓመታት ለመፍትሔ አዳግቷል በሚል ቸል ብሎት የነበረው የኢትዮጵያና ኤርትራ ችግርን በመፍታት ረገድ ጠ/ሚ ዐብይ ያበረከቱት ጉልሕ አስተዋጽኦ ለሌሎች ሀገራት ተነሳሽነት የሚፈጥር እንደሆነ በመጥቀስ በኒውዮርኩ ጉባዔ ላይ የክብር ተጋባዥ መሆን እንደሚገባቸው ነው የተጠቆመው፡፡
5. በፈንድቃ ከተማ በተቀሰቀሰ ግጭት የጣና በለስ ስኳር ኮርፖሬሽን ሶስት ሠራተኞች ተገድለዋል የሚለው ዜና ትክክል አለመሆኑን ፋብሪካው ገለጸ፡፡ የሕዳሴ ግድብ ግንባታ ሥራ አስኪያጅ ስመኘው በቀለ (ኢንጂነር) የቀብር ሥነ ሥርዓት በተፈጸመበት ዕለት መብራት ከመጥፋት ጋር በተያያዘ… በአማራ ክልል፣ አዊ ዞን፣ ፈንድቃ ከተማ የሶስት ሰዎች ሕይወት ማለፉን የገለጸው ስኳር ፋብሪካው፣ ሆኖም ግን ግጭቱ የተከሰተበት ከተማ ከፕሮጀክቱ በ3 ኪሎ ሜትር እንደሚርቅ፣ የሞቱትም የስኳር ኮርፖሬሽኑ ሠራተኞች አለመሆናቸውን አስረድቷል፡፡
6. የብሪታንያ መከላከያ ሚኒስትር ጋቢን ዊሊያምሰን በአዲስ አበባ ከተማ ከአቻቸው ሞቱማ መቃሳ ጋር ተወያዩ፡፡ መከላከያ ሚኒስትሮቹ በአፍሪካ ቀንድ በሚታየው ወታደራዊ እንቅስቃሴ፣ በሶማሊያ ስለሚገኘው የአፍሪካ ሕብረት ሠላም አስከባሪ ሠራዊት እንዲሁም ሽብርተኝነትን በመከላከል ዙሪያ መምከራቸው ተገልጿል፡፡
7. ሶማሊያ በኤርትራ ላይ የተጣለው ማዕቀብ እንዲነሳ መጠየቋን ጂቡቲ ተቃወመች፡፡ በሞቃዲሾ የጂቡቲ ኤምባሲ ባወጣው መግለጫ… ጂቡቲያውያን በሶማሊያ የሠላም አስከባሪነት ተሰማርተው በሚገኙበት ወቅት ኤርትራ ላይ የተጣለው ማዕቀብ እንዲነሳ በሶማሊያ መጠየቁ አሳሳቢ እንደሆነ ገልጿል፡፡ ኤርትራ በተባበሩት መንግስታት ድርጅት የተጣለባት ማዕቀብ እንዲነሳ ኢትዮጵያ ይፋዊ ጥያቄ ባቀረበችበት ወቅትም ከጂቡቲ መንግስት ተመሳሳይ ቅሬታ መሰማቱ አይዘነጋም፡፡
8. የአንጋፋው አርቲስት ፍቃዱ ተክለማርያም የቀብር ሥነ ሥርዓት ዛሬ ከቀትር በኋላ በቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ተፈጸመ፡፡ የቀብር ሥነ ሥርዓቱ ከመከናወኑ አስቀድሞ አድናቂዎቹና የኪነ ጥበብ ቤተሰቦች በተገኙበት በብሔራዊ ቴአትር የስንብት ፕሮግራም ተካሂዷል፡፡ በ62 ዓመት ዕድሜ በኩላሊት ሕመም ያለፈው ፍቃዱ ተክለማርያም ከወጣትነት መጀመሪያ ዕድሜው አንስቶ ከቴአትር መድረክ ሳይለይ ኖሮ አልፏል፡፡
ለወዳጆችዎ ያጋሩ SHARE SHARE SHARE